“የአቶ አንዱአለም ደኅንነት አደጋ ላይ ነው” አንድነት ፓርቲ
በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው በቃሊቲ ማረሚያ ቤት በእስር ላይ የሚገኙት አቶ አንዱአለም አራጌ የካቲት 7 ቀን 2004 ዓ.ም. ከቀኑ በ8፡00 ሰዓት ገደማ ለሕይወታቸው የሚያሰጋ ከባድ ድብደባ የተፈጸመባቸው መሆኑን አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ አስታወቀ፡፡
የፓርቲው አመራሮች ትናንት ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ እንዳስታወቁት፣ ድብደባውን የፈጸመው አቶ አንዱአለም በታሰሩበት ክፍል ውስጥ የታሰረ ኢባስ አስፋው የሚባል ፍርደኛ ሲሆን፣ አቶ አንዱአለም በክፍላቸው ውስጥ የግል ጉዳያቸውን በማከናወን ላይ በነበሩበት ጊዜ ባልታወቀ ምክንያት ድብደባ ጀመረ፡፡ መጀመርያ በእርግጫ ጭንቅላታቸውን መትቶ ከጣላቸው በኋላ፣ በወደቁበት ጫማ ባደረገ እግሩ በሲሚንቶ ወለሉ ላይ ደጋግሞ በመረጋገጥ ራሳቸውን እስከሚስቱ ድረስ ድብደባ የተፈጸመባቸው መሆኑን ከአስተማማኝ ምንጮች መረጃ ማግኘቱን ፓርቲው ገልጿል፡፡ ሕይወታቸው የተረፈውም በክፍሉ ውስጥ በነበሩ ታራሚዎች ገላጋይነት መሆኑን ፓርቲው አክሎ አስታውቋል፡፡
ድብደባውን የፈጸመው ግለሰብ ቀደም ሲል በነፍስ ግድያ ወንጀል ተከስሶ የሞት ፍርድ ተፈርዶበት የነበረ መሆኑንና ኋላ ላይ ግን ፍርዱ ተሻሽሎለት ቅጣቱ ወደ ዕድሜ ልክ እስራት የተለወጠለት መሆኑን የገለጸው አንድነት ፓርቲ፣ በማረሚያ ቤቱ ሌሎች ክፍሎች ውስጥ ለረጅም ዓመታት ታስሮ የነበረው ይህ ፍርደኛ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ አቶ አንዱአለም ወደ አሉበት ክፍል ተዛውሮ እንዲመጣ የተደረገበት ምክንያት አለመታወቁን አስታውቋል፡፡
“አቶ አንዱአለም በተፈጸመበት ድብደባ ምክንያት ከፍተኛ የአካልና የሥነ ልቦና ጉዳት ደርሶበታል፤ ለሕይወቱ በመስጋት እስካሁን ድረስ ወደ ሆስፒታል ለመሄድ አልፈለገም፡፡ ምርመራና የሕክምና ዕርዳታ እንዲያገኝ ለማድረግ ግን በቤተሰብ በኩል ጥረት እየተደረገ እንደሆነ ተገልጿል፤” ይላል የአንድነት ፓርቲ መግለጫ፡፡
የአንድነት ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ዶ/ር ኃይሉ አርዓያ ከጠበቆችና ከአቶ አንዱአለም ወንድም ያገኙትን መረጃ መሠረት አድርገው እንደገለጹት፣ አቶ አንዱአለም በደረሰባቸው ድብደባ ለከፍተኛ የራስ ሕመም የተጋለጡ ሲሆን ራሳቸውን ችለው ለመቆምም ተቸግረዋል፡፡
“የአንድ ሰው ጭንቅላት ከሲሚንቶ ወለል ጋር በተደጋጋሚ ሲረገጥ የውስጥ የጤና ችግር ሊፈጠር ይችላል፡፡ ውጭያዊው ምልክት ሲታይ በዓይኑ ላይ የመበለዝና የመጥቆር ምልክት አለ፡፡ ያለበትን ራስ ምታት ለማስታገስ ራሱን በሻሽ ያስራል፤ ጭንቅላቱ ላይ ምን ጉዳት እንደደረሰበት አይታወቅም፡፡ ምናልባትም ሲቲ ስካን ያስፈልገዋል፤›› ዶ/ር ኃይሉ ብለዋል፡፡ እንደ እርሳቸው ገለጻ፣ አቶ አንዱአለም ወደ ሆስፒታል ሄደው መታከም ያልፈለጉት ሊገሉኝ ይችላሉ የሚል ስጋት ስላደረባቸው ነው፡፡
በ1997 ዓ.ም. የወጣው የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ የወንጀል ሕግ አንቀጽ 110(3) ላይ ውሳኔ ያላገኙ እስረኞች ውሳኔ ካገኙ ሌሎች እስረኞች ጋር እንደማይቀላቀሉ ይደነግጋል፡፡ እንዲሁም በኢፌድሪ ፍትሕ ሚኒስቴር ተሰባስቦና ተተርጉሞ በ1998 ዓ.ም. በታተመውና ኢትዮጵያ ባፀደቀቻቸው ዓለም አቀፍ ሰነዶች አንቀጽ 85(1) ላይ እንደተገለጸው፣ ፍርድ በመጠባበቅ ላይ የሚገኙ እስረኞች በአንድ ክፍል እንደማይታሰሩ ይገልጻል፡፡ የቃሊቲ ማረሚያ ቤት የዕድሜ ልክ እስራት የተፈረደበትን ፍርደኛ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታዩ ካሉ እስረኞች ጋር እንዲታሰር ያደረገበት ምክንያት ግን አልታወቀም፡፡
የአንድነት ፓርቲ ዋና ጸሐፊ አቶ አስራት ጣሴ እንደሚሉት፣ አቶ አንዱአለም ሆነ ተብሎ እንዲደበደብ ሳይደረግ አይቀርም፡፡ “ደብዳቢው አቶ አንዱአለምን ኮረፌ (ጠላ) ጠጣ ሲለው አልጠጣም በማለቱ በተፈጠረ ግጭት ድብደባ አድርሶበታል፡፡ አንዱአለም ጠዋትና ማታ የምግብ አድማ እናድርግ እያለ እስረኞችን ይጨቀጭቃቸው ነበር፤” በሚል በማረሚያ ቤቱ አስተዳደር ተሰጥቷል የተባለው ምክንያት እንዳልተዋጠላቸው ገልጸዋል፡፡
“አንዱአለም ለሰላም ያለው አክብሮት ከልክ በላይ ነው፡፡ [ከምርጫ 97 በኋላ] ከእሱ ጋር አብሬ አንድ ዓመት ታስሬያለሁ፡፡ ቁርስ፣ ምሳና፣ እራት ሲበላ የሚፀልይና የተጣላን ሰው የሚያስታርቅ ሰው ነው፤” በማለት በግል ፀብ ምክንያት ድብደባ ሊደርስበት እንደማይችል የገለጹት አቶ አስራት፣ ኢትዮጵያ አሁን ያለችበት ደረጃ ታዋቂው አፍሪካዊ ደራሲ ቼኔዋ አቼቤ እንዳለው “አገሬ እሪ በይ” የሚያስብል ደረጃ ላይ የደረሰች መሆኗን ተናግረዋል፡፡
በአቶ አንዱአለም ላይ ድብደባ የፈጸመው እስረኛ ከእነ አቶ አንዱአለም ጋር ከነበረበት ክፍል ተወስዶ 300 ያህል ታራሚዎች ወደሚገኙበት ሌላ ቤት የተዛወረ መሆኑን በመግለጫው የጠቆመው አንድነት ፓርቲ፣ አቶ አንዱአለምን የደበደበው ፍርደኛ በዚሁ ቤት ውስጥ ከሚገኘው የአንድነት አመራር አባል ከአቶ ናትናኤል መኮንን ጋር እንዲተኛ መደረጉ አሳሳቢ ጉዳይ መሆኑን፣ በአቶ አንዱአለም ላይ የተፈጸመው ድርጊት በአቶ ናትናኤል ላይም ይፈጸማል የሚል ስጋት እንዳለው አስታውቋል፡፡
አንድ ሰው ድብደባ ሲፈጽም እጁ በካቴና ታስሮ በተለየ ክፍል ውስጥ ሊታሰር እንደሚገባው የገለጹት ዶ/ር ኃይሉ አርዓያ፣ በአቶ አንዱአለም ላይ ጉዳት ያደረሰው ፍርደኛ ግን 300 እስረኞች ወደሚገኙበት ሌላ ክፍል መዛወሩንና በአስገራሚ ሁኔታ ከሌላው የአንድነት አመራር አባል አቶ ናትናኤል መኮንን ጐን እንዲተኛ መደረጉን ተናግረዋል፡፡
“ከሦስት መቶ ሰዎች መካከል ከአቶ ናትናኤል ጐን እንዲተኛ መደረጉ አጋጣሚ ነው?” ሲሉ የሚጠይቁት ዶ/ር ኃይሉ፣ በአቶ አንዱአለም ላይ ሆን ተብሎ የተፈጸመው ድርጊት በአቶ ናትናኤል ላይም ሊፈጸም ይችላል የሚል ስጋት እንዳለ ገልጸዋል፡፡
የአንድነት ፓርቲ ሊቀመንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ በበኩላቸው፣ የአፍሪካ ኅብረት ጽሕፈት ቤት በተመረቀበት ጊዜ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ዓለም በቃኝ እስር ቤት የነበረበት ቦታ ለአፍሪካ ኅብረት ጽሕፈት ቤት መስጠቱን አስመልክተው የተናገሩት ነገር፣ የአገሪቱን ተጨባጭ ሁኔታ እንደማያመለክት ገልጸዋል፡፡ በ1997 ምርጫ ሰዎች ያለፍርድ የታሰሩበት ሁኔታ መኖሩን የገለጹት ዶ/ር ነጋሶ፣ በአሁኑ ጊዜ ደግሞ በእስር ላይ የሚገኙ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ አባላት በተለያዩ መንገዶች ስድብ፣ ዛቻና ጥቃት እየደረሰባቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የአንድነት ፓርቲ የድርጅት ጉዳይ ኃላፊ ኢንጅነር ዘለቀ ረዲ የአገሪቱ ወንጀለኛ ሕግ ፍርደኞች ከተጠርጣሪ እስረኞች ጋር ሊታሰሩ እንደማይገባ እየደነገገ፣ ሕጉ ተሽሮ ዕድሜ ልክ እስራት የተፈረደበት ሰው በክርክር ላይ ከሚገኙ ታሳሪዎች ጋር እንዲቀላቀል የተደረገበት ምክንያት እንቆቅልሽ መሆኑን ይገልጻሉ፡፡
“ማረሚያ ቤቱ ሕግ ጥሷል፤ በእነዚህ አገር ሕግ የሚወጣው መንግሥት በማይፈልጋቸው ላይ እንዲፈጽም ነውን?” የሚሉት ኢንጅነር ዘለቀ፣ መንግሥት በአሁኑ ጊዜ የሚሠራው ሥራ ሁሉ ተቃዋሚ ፓርቲዎች እንዳይንቀሳቀሱ ለማድረግ ታስቦ የሚከናወን ይመስላል ብለዋል፡፡
በመንግሥት በኩል ከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እየተፈጸመ ነው የሚለው አንድነት ፓርቲ ወደፊት የሚያካሂደውን የፖለቲካ ትግል በተመለከተ ጥያቄ የቀረበላቸው ዶ/ር ነጋሶ፣ ፓርቲው የብሔራዊ ምክር ቤት አባላትን ካወያየ በኋላ የተለያዩ ሰላማዊ የትግል ዓይነቶችን ከመቀጠል ውጪ ትግሉን እንደማያቆም ተናግረዋል፡፡
አቶ አስራት ጣሴ በበኩላቸው፣ “ዘላለም ጋዜጣዊ መግለጫ እየሰጠን እስከየት ድረስ እንቀጥላለን ለሚለው ጥያቄ መልስ መስጠት ያለበት የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው፤” ብለዋል፡፡ “ሚስማርና ታጋይ ሲመታ ይጠብቃል፤ ታጋይ ይሞታል እንጂ ትግል አይሞትም፤” ያሉት ኢንጂነር ዘለቀ በበኩላቸው፣ በአንድነት ፓርቲ አመራር አባላት ላይ የሚደርሰው ጥቃት ሰላማዊ ትግሉን እንደሚያጠናክረው ይገልጻሉ፡፡ እርሳቸው እንዳሉት፣ አቶ አንዱአለም ከታሰሩ በኋላ በርካታ ወጣቶች የፓርቲው አባል ሆነው መመዝገባቸውን የሚያመለክተው መንግሥት በደል እየፈጸመ በሄደ ቁጥር ለትግል የሚነሳው ሕዝብ ቁጥር እየጨመረ እንደሚመጣ ነው፡፡
“በአቶ አንዱአለም ላይ ድብደባ ያደረሰውን ፍርደኛ ለመክሰስ አስባችኋል ወይ?” በሚል ከጋዜጠኛ ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ የሰጡት አመራሮቹ፣ በክስ የሚመጣ ለውጥ ይኖራል የሚል እምነት ባይኖራቸውም አቶ አንዱአለም ፈቃደኛ ከሆኑ ለመዝገብና ለታሪክ ሲባል ፓርቲው ክስ ሊመሠርት እንደሚችል አስታውቀዋል፡፡ የፓርቲው አመራሮች እንዳሉት፣ ማረሚያ ቤቱ በፍርደኛው ላይ አስተዳደራዊ ዕርምጃ ከመውሰድ ውጭ ክስ ሊመሠረትበት እንደማይችል የማረሚያ ቤቱ አስተዳዳሪዎች ለአቶ አንዱአለም ጠበቆች ገልጸውላቸዋል፡፡


