– ከ100 በላይ አመራሮችና ሠራተኞች በቁጥጥር ሥር ውለዋል
ተቀጥረው የሚሠሩበትን የመንግሥት ሥራና ኃላፊነት ወደ ጎን በመተው፣ የራሳቸውን ጥቅም በማስቀደም ሙስና በመፈጸምና ለመልካም አስተዳደር እንቅፋት በመሆን የተጠረጠሩ በተለያዩ የሥራ ኃላፊነቶች የነበሩ 22 አመራሮች፣ በቁጥጥር ሥር ውለው ምርመራ እየተደረገባቸው ነው፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ የልማት እንቅስቃሴዎች በአግባቡ እንዳይከናወኑ እንቅፋት በመሆንና በተለያዩ የመንግሥት ተቋማት ውስጥ ኃላፊ ሆነው ሲሠሩ፣ በተለያየ ደረጃ የሙስና ተግባር የፈጸሙ መሆናቸውን ፖሊስ ተጠርጣሪዎቹን ለፍርድ ቤት ሲያቀርብ አስረድቷል፡፡
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመቀናጀት ከታኅሳስ 7 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ ባደረገው ዘመቻ፣ በተለያዩ የከተማው አስተዳደር መሥሪያ ቤቶች ውስጥ ከተፈጸሙ የሙስና ወንጀሎች ጋር በተያያዘ የተጠረጠሩ 125 አመራሮችንና ሠራተኞችን መያዙም ታውቋል፡፡
በሕገወጥ መንገድ የተሽከርካሪ ሰሌዳ በመስጠት፣ በሌሎች ሰዎች ስም መንጃ ፈቃድ በመስጠት፣ የመንግሥትን ቤቶች ወደ ግል በማዞር፣ የመንግሥት ገንዘብ በማጉደል፣ ያለጨረታ ከሕግ ውጪ ጨረታዎችን በመስጠትና በሌሎች የወንጀል ድርጊቶች ተጠርጥረው መያዛቸውን ፖሊስ ገልጿል፡፡
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን ዕርምጃውን እንደቀጠለ፣ በቁጥጥር ሥር ያዋላቸውን ፍርድ ቤት እያቀረበ እንደሆነና ሌሎች ያልተያዙ ተጠርጣሪዎችን በመከታተል ላይ እንደሆነ አስታውቋል፡፡
በቁጥጥር ሥር የዋሉትን ተጠርጣሪዎች ከታኅሳስ 8 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ ፍርድ ቤት በማቅረብ የ14 ቀናት ጊዜ ቀጠሮ ጠይቆ በምርመራ ላይ መሆኑም ታውቋል፡፡