[የክቡር ሚኒስትሩ ወዳጅ ከውጭ አይፓድ ልኮላቸዋል፡፡ ክቡር ሚኒስትሩ የተላከላቸው ዕቃ ምን እንደሆነ ስላልገባቸው አማካሪያቸውን አስጠሩት]
– ፈለጉኝ ክቡር ሚኒስትር?
– በጣም ነው እንጂ የፈለኩህ፡፡
– ምን ፈልገው ነው?
– አንድ ነገር እንድትረዳኝ ነው፡፡
– ብዙ ሥራ ግን አለብኝ፡፡
– ሥራ የምሰጥህ እኔ መሆኔን ረሳኸው እንዴ?
– አይ ማለቴ የግል ሥራ እንዳያሠሩኝ ብዬ ነው፡፡
– የግል ሆነ የጋራ እሱ አይመለከትህም፡፡
– ምን አሉኝ?
– አሁን ና እዚህ አጠገቤ ቁጭ በል፡፡
– ምን ፈልገው ነው ክቡር ሚኒስትር?
– ምንድን ነው ይኼ?
– ይኼማ አይፓድ ነው፡፡
– ምንድን ነው እሱ ደግሞ?
– ኧረ ብዙ ጥቅም አለው፡፡
– እኮ ምን?
– ለምሳሌ በዚህ ኖት መያዝ ይችላሉ፡፡
– ወረቀትና እስክሪብቶ አለ አይደል እንዴ?
– አሁን እኮ ኢንቫሮመንት ፍሬንድሊ ሆነው ብዙ ወረቀት መጠቀም ማቆም አለብዎት፡፡
– ሌላ ምን ጥቅም አለው?
– ኢንተርኔትም ያስጠቅማል፡፡
– ይኼማ ያደድብሃል ማለት ነው፡፡
– እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
– ኢተርኔት ከተጠቀምክ ብዙ አታነብማ፡፡
– እንዴ ክቡር ሚኒስትር ኢንተርኔት ላይ እኮ ብዙ የሚነበብ ነገር አለ?
– ምን ፌስቡክና ወሬ አይደለም እንዴ ያለው?
– ኧረ በዩ ቲዩብ ቪዲዮ ምናምን ማየት ይችላሉ፡፡
– ቪዲዮም ማየት እችላለሁ?
– አዎን ክቡር ሚኒስትር፡፡
– አሁን ጥቁር ፍቅርንና ዛራና ቻንድራን እዛ ቲዩብ ላይ አገኘዋለሁ?
– እሱን እንኳን የራሳቸው ዌብሳይት ላይ ነው የሚያገኙት፡፡
– ይህቺ ነገር ጠቃሚ ሳትሆን አልቀረችም፡፡
– ከፈለጉም ፎቶና ቪዲዮ ማንሳት ይችላሉ፡፡
– በዚህ?
– አዎና፡፡
– በቃ እኔማ ምን እንደማደርግ አውቃለሁ፡፡
– ምን ሊያደርጉ?
– በቃ እነዛ ስሜን የሚያጠፉትን ሰዎች በዚህ ቪዲዮ ቀድቻቸው እከሳቸዋለሁ፡፡
– እነሱ እኮ ስምዎትን እያጠፉ አይደለም፡፡
– ታዲያ ሙሰኛ ነው እያሉ ምን እያደረጉኝ ነው?
– መረጃ እኮ አላቸው፡፡
– መረጃውን ያቅርቡዋ፡፡
– ኧረ ይተዉ ክቡር ሚኒስትር፡፡
– ለማንኛውም እስቲ ክፈተው፡፡
– ይኸው ክቡር ሚኒስትር፡፡
– እንዴት ነው የማበራው?
– ይኸው አብርቼዋለሁ፡፡
– ከዛ ምንድን ነው የማደርገው?
– የፈለጉት ቦታ ሲነኩት ይሠራል፡፡
– ይኸው ነካሁት፡፡
– እሱ እኮ ጀርባው ነው፡፡
– ታዲያ የፈለክበት ቦታ ንካው አላልከኝም እንዴ?
– ክቡር ሚኒስትር አንድ ችግር እንዳለብዎት ተረዳሁ፡፡
– የምን ችግር?
– የንቃተ ህሊና!
[ክቡር ሚኒስትሩ ከአፍሪካ አገር ከመጣ ሌላ ሚኒስትር ጋር ምሳ እየበሉ ነው]
– እንዴት ነዎት ክቡር ሚኒስትር?
– እንዴት ነህ ባክህ?
– አለን አለን፡፡
– ለሥራ መጥተህ ነው?
– ኧረ ለመዝናናት ነው የመጣሁት፡፡
– ለነገሩ ኢትዮጵያ እኮ ለመዝናናት ትመቻለች፡፡
– እንዴ በደንብ እንጂ ክቡር ሚኒስትር፡፡
– ታዲያ የት ነው ያረፍከው?
– እዚህ እኮ ቤት ገዝቻለሁ፡፡
– ጥሩ አድርገሃል፡፡
– ኢንቨስትመንት ውስጥም እኮ ገብቻለሁ፡፡
– ባለሀብት ሆነሃላ?
– ያው እንግዲህ ተያይዘነዋል፡፡
– ለመሆኑ ገንዘቡን ከየት አምጥተህ ነው?
– ምን እኛ አገር ሙሰኛ ያልሆነ ባለሥልጣን አለ እንዴ?
– የእኛው ጐራ ነሃ?
– በሚገባ ክቡር ሚኒስትር፡፡
– ለመሆኑ ምን ምን ትሠራለህ?
– እንዴ ክቡር ሚኒስትር የሎጂስቲክስ ሥራው ውስጥ ታዋቂ የሆነ ድርጅት አለኝ፡፡
– ምን እኔም እኮ እዛ ዘርፍ ውስጥ አለሁ፣ ግን የአንተን ድርጅት አላውቀውም፡፡
– ከዛም ባሻገር በሪል ስቴት ዘርፉ እየተመነደገ ያለ ድርጅት አለኝ፡፡
– አየህ የማላውቀው ለዛ ነዋ፣ የእኔ ድርጅት ተመንድጐ ጨርሷል፡፡
– ሌላስ ምን ይሠራሉ?
– አሁን ደግሞ ብራንድ ሆቴሎች አገራችን እየበዙ ስለመጡ፣ ጭስ አልባውን ኢንዱስትሪ ለመቀላቀል አስቤያለሁ፡፡
– በነገራችን ላይ ክቡር ሚኒስትር…
– ምንድን ነው?
– ፕራይቬት ጄት ልገዛ ነው፡፡
– እኔ እንኳን የአቪዬሽን ኢንዱስትሪው መሽቆልቆል ላይ ስላለ ያሰብኩት ሌላ ነገር ለመግዛት ነው፡፡
– ምን ሊገዙ ነው?
– መርከብ!
[የክቡር ሚኒስትሩ የቅርብ ዘመድ ከገጠር ቤታቸው መጥቷል]
– እንዴት ነዎት ጋሼ?
– ምን ልታደርግ መጣህ?
– ጋሼ ኑሮ በጣም አስቸገረኝ፡፡
– አሁንም በቃ መጠጣት አላቆምክም አይደል?
– ወድጄ አይደለም እኮ የምጠጣው ጋሼ፡፡
– ለምንድን ነው የምትጠጣው?
– በቃ የገጠር ኑሮ ጠብ የሚል ነገር የለውም፡፡
– ለምን አትሠራም?
– ኧረ እኔ ሥራ አስጠልቶኛል፡፡
– ለመሆኑ ስንት ነው ዕድሜህ?
– 31 ሞልቶኛል፡፡
– በዚህ ዕድሜህ ነው ሥራ ያስጠላህ?
– ምን እንዳማረኝ ያውቃሉ ጋሼ?
– ምንድን ነው ያማረህ?
– በቃ ሳልሠራ እንደ እርሶ እንደዚህ የተንፈላሰሰ ቤት ውስጥ መኖር፣ በቃ እሱ ነው ያማረኝ፡፡
– መቼም የእናትህ አደራ የሚረሳ አይደለም፡፡
– በቃ ጋሼ ተንቀባርሬ እንድኖር ያድርጉኝ፡፡
– ስማ አሁን አንድ ሥራ እሰጥሃለሁ፡፡
– ምንድን ነው ሥራው?
– አንድ የሚሸጥ መሬት አለ፡፡
– እሺ ጋሼ፡፡
– ስለዚህ እኔ የምልክህ ገዢ ጋር ሄደህ በ50 ሚሊዮን ብር የሚሸጥ መሬት አለ ትለዋለህ፡፡
– መሬት ነው አገር ነው በ50 ሚሊዮን ብር የሚሸጠው?
– አንድ ቪላ ቤት ነው፡፡
– ብሩ በዛ ብዬ ነው፡፡
– ያልተጠየከውን አትቀባጥር፡፡
– ይቅርታ ጋሼ፡፡
– ከዛም መሬቱን የሚሸጠው ሰውዬ ጋ ሄደህ ቦታውን በ50 ሚሊዮን ብር የሚገዛ ሰው አግኝቼልሃለሁ ትለዋለህ፡፡
– እሺ ጋሼ፡፡
– ከዛ በቃ አንድ ሚሊዮን ብር የድለላ ታገኛለህ፡፡
– ወይ ግሩም፡፡
– ገብቶሃል?
– ምንም አልገባኝም፡፡
– መጀመሪያ ገዢውን ታገኛለህ፡፡
– እሺ፡፡
– ከዛም በ50 ሚሊዮን ብር የሚሸጥ…
– አገር አለ እለዋለሁ፡፡
– መሬት ነው አገር አይደለም የሚሸጠው፡፡
– እሺ ይቅርታ፡፡
– ከዛ ከሻጭ ጋር አገናኝተህ አንድ ሚሊዮን ብርህን ትቀበላለህ፡፡
– እሺ ጋሼ አመሰግናለሁ፡፡
[የክቡር ሚኒስትሩ የቅርብ ዘመድ የመሬት ሽያጭ ኮሚሽኑን ከተቀበለ ከአራት ወራት በኋላ ቤታቸው መጣ]
– አሁን ደግሞ ምን ፈለክ?
– ጋሼ አንድ ችግር ገጥሞኝ ነው፡፡
– የድለላውን ብር አልተቀበልክም እንዴ?
– ኧረ ተቀብያለሁ፡፡
– እኮ የምን ችግር ነው የምታወራው ታዲያ?
– ብሩ ጠፋብኝ፡፡
– ምን ሆኖ?
– በቃ የከተማ ሰው አንዱ አበድረኝ ሲለኝ፣ አንዱ ጋብዘኝ ሲለኝ ብሯን አሟጠጥኳት፡፡
– አንድ ሚሊዮኑን በአራት ወራት ውስጥ ጨረስከው?
– ኧረ ያጠፋሁትማ በሁለት ወራት ነው፡፡
– ታዲያ የት ነበርክ እስካሁን?
– ጋሼ የእርሶን ፊት የማይበት አቅም አልነበረኝምና ለዛ ነው የጠፋሁት፡፡
– ለማንኛውም አንድ ስልክ ልደውል፡፡
[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ መኪና አስመጪ ጋ ደወሉ]
– ጤና ይስጥልኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡
– በቃ አንተ የፈለከውን ካገኘህ በኋላ ጠፋህ አይደል?
– ኧረ ክቡር ሚኒስትር ምን እጠፋለሁ? በጣም ስፈልግዎት ነበር፡፡
– ያን ሁሉ ውለታ አድርጌልህ በዛው ትጠፋለህ?
– ኧረ ክቡር ሚኒስትር ምን ላድርግልዎት?
– አምስት ሲኖ ትራኮች ፈልጌ ነበር፡፡
– ዛሬውኑ በስሞት አዘዋውርልዎታለሁ፡፡
– በእኔ ስም አይሆንም በሌላ ስም ነው የሚሆነው፡፡
– በማን ስም ይደረግ?
[ክቡር ሚኒስትሩ አስመጪው ስልኩን እንዲይዘው አድርገው፣ ዘመዳቸውን ማናገር ጀመሩ]
– ስምህ ማን ነበር?
– ድፋባቸው ብላባቸው፡፡
[ክቡር ሚኒስትሩ ወደ ስልኩ ተመለሱ]
– ድፋባቸው ብላባቸው፡፡
– ማን አሉኝ ክቡር ሚኒስትር?
– ድፋባቸው ብላባቸው፡፡
– ስሙ ግን ፀረ ልማታዊ ይመስላል፡፡
– በቃ በዚህ ስም አድርጋቸው፡፡
[የክቡር ሚኒስትሩ ዘመድ መኪኖቹን ከወሰደ በኋላ ድጋሚ ከስሮ መጣ]
– መቼም አሁን የመጣኸው ልትጋብዘኝ ነው?
– አይ ጋሼ አንድ ነገር ገጥሞኝ ነው፡፡
– መኪኖቹን አልወሰድክም እንዴ?
– ኧረ ወስጄ ሥራም ጀምረዋል፡፡
– ታዲያ ሥራ ከጀመሩ ምን ትፈልጋለህ?
– ከዛ በኋላ መቼም የከተማ ሰው አንድ ክፉ ነገር አስተማረኝ፡፡
– ምን ተማርክ?
– ቁማር ተምሬ ጋሼ በቃ መኪኖቹን ተበላሁ፡፡
– ምን?
– አዎን ጋሼ በካርታ መኪኖቹን ተበላሁ፡፡
– የሠራህበት ገንዘብስ?
– መኪኖቹን ለማስመለስ ስጫወት እሱንም ተበላሁ፡፡
– ወይ ጣጣ!
[ክቡር ሚኒስትሩ ቤት ሲገቡ ሚስታቸውን አገኟቸው]
– ምን ሆነህ ነው የተናደድክ ትመስላለህ?
– ምን ባክሽ አቃጥሎኝ ነዋ፡፡
– እሳት ነው?
– ኧረ ይኼ ድፋባቸው ነው እንጂ፡፡
– ምን ደፋብህ?
– ይኸው ሥራ የለኝም ብሎ በድለላ ያሰጠሁትን አንድ ሚሊዮን ብር በሁለት ወራት ውስጥ አጠፋው፡፡
– ምን ችግር አለው አንተ አንድ ሚሊዮን ብር በወር አይደል እንዴ የምታጠፋው?
– እኔ ታዲያ መቶ ሚሊዮን ኖሮኝ እኮ ነው አንድ ሚሊዮን የማጠፋው፣ እርሱ እንዴት አንድ ሚሊዮን ኖሮት አንዷን ያጠፋታል?
– እሱስ ልክ ነህ፡፡
– ከዛ ደግሞ አምስት ሲኖ ትራክ ሰጥቼው እነርሱንም በቁማር ተበላ፡፡
– አንተ ዋነኛው የከተማው ቁማርተኛ አይደለህ እንዴ?
– ቢሆንም እኔ ዋናዬን ይዤ ነው የምጫወተው፡፡
– ችግሩ እኮ በአንድ ምሽት ሚሊየነሮችን መፍጠርህ ነው፡፡
– ይኼማ የዕድገታችን መገለጫ ነው፡፡
– የተገኘውም ገንዘብ እኮ በአንድ ምሽት እየጠፋ ነው፡፡
– እሱ እኮ ነው ግራ ያጋባኝ፡፡
– እሱማ የምን መገለጫ እንደሆነ እኔ ገብቶኛል፡፡
– የምን መገለጫ ነው?
– የጥፋታችሁ!