ከሚቀጥለው ዓመት ጀምሮ በመሀል አዲስ አበባ የሚገኙ ቁልፍ ቦታዎችን እንዲያለማ ሥልጣን የተሰጠው ‹‹የአዲስ አበባ ማዕከላትና ኮሪደሮች ኮርፖሬሽን››፣ ከነበሩበት ቦታ የሚፈናቀሉ ነዋሪዎች ወደነበሩበት ተመልሰው የሚቋቋሙበትን መንገድ እንደሚከታተል ተመለከተ፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ድሪባ ኩማ ለከተማው ምክር ቤት ባቀረቡት የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ላይ እንደገለጹት፣ የመልሶ ማልማት ሥራ የሚካሄድበት የአካባቢ ነዋሪዎችን አፈናቅሎ ሳይሆን አካቶ መሆን ይኖርበታል፡፡
‹‹ከመልሶ ማልማት አንፃር የአካባቢ ነዋሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ አቅጣጫ በመከተል ማስተር ፕላኑ ባስቀመጠው መንገድ ለመጓዝ ቅድመ ዝግጅት እያደረግን ነው፤›› በማለት ከንቲባ ድሪባ ገልጸው፣ ‹‹ከዚህ በኋላ የሚካሄደው የመልሶ ማልማት የትኩረት አቅጣጫ የከተማው ማዕከል ላይ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ የመልሶ ማልማት ፕሮግራሙ አሁን ካለው ኋላቀር አሠራር ወጥቶ በፕሮጀክት መልክ በዕቅድና በቂ ቅድመ ዝግጅት አድርጎ የሚሠራ ሲሆን፣ ሥራውን በባለቤትነት የሚፈጽም ኮርፖሬሽን ተቋቁሞ ወደ ሥራ ተገብቷል፤›› በማለት ከንቲባው በሪፖርታቸው ገልጸዋል፡፡
ከንቲባው እንዳብራሩት፣ በአዲሱ የመልሶ ማልማት ሥራ መምጣት ያለባቸው ሁለት መሠረታዊ ለውጦች አሉ፡፡ የመጀመሪያው የሚካሄደው ልማት ዋነኛ ማጠንጠኛ የነዋሪዎች ተጠቃሚነት ጉዳይ መሆን አለበት፡፡
‹‹የመልሶ ማልማት ሥራ ነዋሪዎችን የሚያካትና የሚያሳትፍ እንዲሆን፣ ከኖሩበት ጎስቋላ ኑሮ የሚያላቅቅና ወደ ተሻለ ደረጃ የሚያደርስ ስለመሆኑ እርግጠኛ መኮን አለበት፤›› በማለት ከንቲባው አስረድተዋል፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ከንቲባው እንዳብራሩት የመልሶ ማልማት ሥራ የከተማ ማዕከሎች ላይ የሚያተኩር ሆኖ በቂ ቅድመ ዝግጅት የተደረገበት መሆኑን ማረጋገጥ ስለሚገባ፣ የከተማ አስተዳደሩ ከየትኛውም ሥራ በላይ የመልሶ ማልማት ሥራ ውስጥ የልማት ተነሽዎችን ጉዳይ በልዩ ትኩረት ይታያል ብለዋል፡፡
በአርከበ ዕቁባይ (ዶ/ር) የሚመራው የቀድሞ የአዲስ አበባ ከተማ ጊዜያዊ አስተዳደር የመልሶ ማልማት ፕሮግራም ከጀመረ ጊዜ አንስቶ ላለፉት 13 ዓመታት በርካታ ነዋሪዎች ከነበሩበት ተፈናቅለው፣ በአብዛኛው በከተማ ዳርቻዎች በተሠሩ ኮንዶሚኒየም ቤቶች ይኖራሉ፡፡ ይህም ለተለያዩ ማኅበራዊ ቀውሶች እንዳጋለጣቸው ነዋሪዎች ባገኙት አጋጣሚ ሲገልጹ ቆይተዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ ምትክ ቦታና ካሳ አከፋፈል ላይ ከፍተኛ ቅሬታዎች ሲነሱ የቆዩ ሲሆን፣ ይህም በነዋሪዎችና በመንግሥት መካከል ከፍተኛ አለመግባባት ፈጥሮ ቆይቷል፡፡ ችግሩን ለመፍታት ያስችላል የተባለው የማዕከላትና ኮሪደሮች ልማት ኮርፖሬሽን እነዚህ ችግሮች ዳግም እንዳይከሰቱ ያደርጋል ተብሏል፡፡
ኮርፖሬሽኑ ከተሰጡት ሥልጣንና ኃላፊነቶች መካከል ለአልሚዎች መሬት ማስተላለፍ፣ የማዕከላትና የኮሪደሮች ልማት የሚካሄድባቸው ቦታዎች በፕላን ቅደም ተከተል በሕግ የማስለቀቅ፣ በሕጉ መሠረት ለተነሺዎች ካሳ የመክፈል፣ ምትክ ቦታና ቤት ለሚያስፈልጋቸው መስጠት፣ መልማት አለባቸው ለተባሉ ቦታዎች ከማንኛውም ሕጋዊ የይገባኛል ክርክር ነፃ ማድረግ የሚሉ ተጠቃሾች ናቸው፡፡
አዲሱ የመልሶ ማልማት ፕሮግራም ለነዋሪዎች ቅድሚያ የሚሰጥ እንደሆነ፣ በዋናነት ነዋሪዎች በተፈናቀሉት ቦታ ላይ በሚካሄደው ልማት ተጠቃሚ ይሆናሉ ተብሏል፡፡