አዲስ አበባ የዓለም አቀፍ እግር ኳስ ማኅበር (ፊፋ) 70ኛ ጉባዔን ለማስተናገድ መሰናዶ ጀምራለች፡፡ ፊፋም ኢትዮጵያ እያደረገች ያለውን ዝግጅት ሰሞኑን መመልከቱ ታውቋል፡፡
በመጪው ግንቦት ወር መጨረሻ በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ ለሚጠበቀው የፊፋ ጉባዔ፣ በአገር አቀፍ ደረጃ የተቋቋመው ብሔራዊ የዝግጅት ኮሚቴ ከሁለት ወር በፊት ሥራውን የጀመረ መሆኑን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል፡፡ ይህንኑ ተከትሎ የፊፋ ልዑካን ቡድን ከየካቲት 16 እስከ 20 ቀን 2012 ዓ.ም. ድረስ በአዲስ አበባ ባደረገው ቆይታ ከብሔራዊ ፌዴሬሽኑ አመራሮችና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው የመንግሥት ኃላፊዎች ጋር በጋራና በተናጠል ስብሰባ ማድረጉ ተነግሯል፡፡
ለአንድ ሳምንት ያህል በአዲስ አበባ ቆይታ ያደረገው የፊፋ ልዑካን ቡድን በዋናነት የፊፋን ጉባዔ ውጤታማ ማድረግ በሚቻልባቸው ጉዳዮች ዙሪያ ተነጋግሯል፡፡ ፊፋ ከሁለት ዓመት በፊት የዚህ ተመሳሳይ ስብሰባ በአዲስ አበባ ለማድረግ ፕሮግራም ይዞ የነበረ ቢሆንም፣ ሆቴል መሰል ቅድመ ሁኔታዎች “አልተሟሉልኝም” በሚል ስብሰባውን ወደ ደቡብ አፍሪካ ማዛወሩ አይዘነጋም፡፡
ከፊፋ ልዑካን ቡድን ጋር የተደረገውን ውይይት አስመልክቶ ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ እንዳስታወቀው ከሆነ፣ በአሁኑ ወቅት በፕሬዚዳንት ሳህለ ወርቅ ዘውዴ የሚመራ ብሔራዊ የዝግጅት ኮሚቴ እንዲቋቋም ተደርጎ እንቅስቃሴ ተጀምሯል፡፡ በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኅብረት ስብሰባዎችን ጨምሮ ልዩ ልዩ የተባበሩት መንግሥታት ስብሰባዎችንና የዓለም ኢኮኖሚክ ፎረምን ያስተናገደች ከተማ እንደመሆኗ ብሔራዊ ዝግጅት ኮሚቴው ስብሰባውን ካዘጋጁት አካላት ጋር በመገናኘት የልምድ ልውውጥ ስለማድረጉ ጭምር ፌዴሬሽኑ በላከው መግለጫ ተካቷል፡፡
ከግንቦት 28 እስከ ሰኔ 2 ቀን 2012 ዓ.ም. ድረስ በአዲስ አበባ ይካሄዳል ተብሎ በሚጠበቀው የፊፋ ጉባዔ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ የስብሰባው ተሳታፊ ቁጥር በውል እንደማይታወቅ ያስታወቀው የፌዴሬሽኑ መግለጫ፣ ለስብሰባው የሚያስፈልጉ ግብዓቶች መጉላላት እንዳይፈጠር ከገቢዎችና ጉምሩክ ኃላፊዎች ጋር ውይይት ተደርጓል፡፡ ሆቴልና ቪዛ የመሳሰሉት ጉዳዮችም በመጠናቀቅ ላይ መሆናቸው ተነግሯል፡፡